loading
የኢትዮጵያና የቻይና የንግድ ፎረም በአዲስ አበባ ተካሄደ

አርትስ 14/03/2011

በፎረሙ ከመቶ በላይ የቻይና ትልልቅ ኩባንያ ባለቤቶች ተሳታፊ ሆነዋል።

ከሁለት ቀናት በፊት አዲስ አበባ የገባው የቻይና ኩባንያዎች ልዑካን ቡድን በቆይታው የሁለትዮሽ ግንኙነቱን ከማጠናከር በተጨማሪ፤ በአዲስ አበባና አካባቢዋ የሚገኙ የኢንቨስትመንት ስፍራዎችን ጎብኝቷል፡፡

በቆይታቸውም በኢትዮጵያ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ማብራሪያ ተደርጎላቸዋል፡፡

በቻይና የኢትዮጵያ ቆንስላ ጄኔራል አምባሳደር ሙሌ ታረቀኝ እንዳሉት የልዑካን ቡድኑ በቆይታው ደስተኛ ነበር። ለጉብኝት ከመጡት ኩባንያዎች ውስጥ እዚሁ ቀርተው ሊሰማሩባቸው ባሰቧቸው የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ጥናት ለማድረግ የወሰኑ ኩባንያዎችም አሉ ብለዋል።

ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር ያላት የንግድ የባህልና የኢንቨስትመንት ትስስር ከመቼውም ጊዜ በላይ ተጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት ደግሞ የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር አክሊሉ ሃይለሚካኤል ናቸው፡፡

ዶክተር አክሊሉ እንዳሉት መንግስት ትልልቅ የመንግስት ተቋማትን ወደ ግሉ ዘርፍ የማዘዋወር አላማ እንዳለው ባሳወቀበት ወቅት የቻይና ባለሃብቶች  ዝግጁነታቸውን ገልጸዋል።

በጉብኝታቸው ደስተኛ መሆናቸውን ለአርትስ ቲቪ የተናገሩት ባለሃብቶቹ  በቂ የመንገድ መሰረተ ልማት አለመኖርና የቴሌኮሙኒኬሽን ኔትወርክ በበቂ ሁኔታ አለመኖር የኢንቨስተሮችን ተነሳሽነት እንዳይቀንስ ስጋት አለን ብለዋል። መንግስት ለዚህ ችግር ትኩረት ቢሰጠው መልካም እንደሆነም ገልጸዋል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *